ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች ተማሪዎቻችሁን አዘጋጁ! – ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ከኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋር በነበራው ቃለ-ምልልስ በቲክቫህ ኢትዮጵያ የተዘጋጀ
የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ከትምህርት ሚኒስቴር ክቡር ሚኒስትር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋን በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መውጫ ፈተና ዙርያ ማብራርያ እንዲሰጡበት ያደረገ ሲሆን በቃለ-ምልልሳቸው የነበረውን ጥቅል ሃሳብ ቲክቫህ-ኢትዮጵያ የሚከተለውን ዘገባ አውጥቷል፡፡ መልካም ቆይታ!!
“ፈተናው የሚቀር አይደለም፤ ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች ተማሪዎቻችሁን አዘጋጁ!”
– ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ
የመውጫ ፈተና በ2015 ዓ/ም መሰጠት ይጀምራል። ይህን በተመለከተ ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ለኢፕድ ከሰጡት ማብራሪያ ፦
” … በሙሉ አቅማችን እየተዘጋጀን ነው። የሚቀር ነገር አይደለም ፤ 2015 ትምህርት ዘመን ማብቂያ ላይ ፤ ከዚህ በፊት እንደነበረው ዝም ብሎ ዲግሪ የሚሰጥበት ነገር ሀገሪቱን በጣም ክፉኛ ጎድቷታል የሚል እምነት አለን። ይሄንንም ከዩኒቨርሲቲ ፕሬዜዳንቶች ጋር፣ ከግል ኮሌጆች ፕሬዜዳንቶች እና ኃላፊዎች ባለቤቶች ጋር ፣ ከዩኒቨርሲቲ መምህራን እና ተማሪዎች ጋር ሰፊ ውይይት ያደረግንበት ነው።
ይሄ አዲስ ሀሳብ አይደለም አተገባበሩ ነው አዲስ የሆነው። ከዚህ በፊት ተሞክሮ ተቃውሞ ስለንበር ነው የተተወው። የህግና የህክምና ትምህርቶችን ብቻ እንዲሰጡት አድርጎ አሁንም እየተሰጡ ሌሎች በሙሉ ተትተው ነበር።
አሁን ግን በአጠቃላይ ከከፍተኛ ትምህርት ጥራት ችግር ጋር በተገናኘ ምንም ልንወጣው የማንችለው እና ያን ጥራት ለማስተካከል ዩኒቨርሲቲዎቹ በራሳቸው ባስተማሩበት እና እራሳቸው በሰጡት ፈተና ብቻ የሚለኩበት ሁኔታ ከጀርባው ያለ ጠንካራ የሞራል መሰረት ይጠይቃል።
ዩኒቨርሲቲዎቹ እራሳቸው ድግሪ ስንሰጥ ለማህበረሰቡ ይሄ ሰው እንዲህ እንዲህ አይነት ትምህርቶችን፣ እውቀቶችና ክህሎቶች አሉት ብለን ነው እየነገርን ያለነው።
… ከዚህ በፊት አንዱ የነበረው ችግር ማሳለፍ የሚባል ነገር አለ። ዝም ብሎ ማሳለፍ ምክንያቱም ተማሪዎች ከወደቁ የትምህርት ክፍሉን ድክመት ያሳያል እየተባለ ሲሳራበት የነበረው ነገር ምን ያህል ሀገሪቱን እንደጎዳት አሁን ለውይይትም የሚቀርብ አይደለም።
እኔ በዚህ ጉዳይ ባለፉት ሰባት (7) ወራት በትምህርት ዘርፍ ከሚሰሩ የዩኒቨርሲቲ ፕሬዜዳንቶች የግል ኮሌጆች ባለቤቶች እንደዚህ አይን ያወጣ የለም መሆን የለበትም የሚል ክርክር አልሰማሁም። ሁሌ የሚሰማው ለምን በኛ ጊዜ ? ለምን ባንተ ጊዜ ለምን በሌላውስ ሰው ጊዜ የሚለውን ልትመልስ አትችልም ይሄ ዝም ብሎ ደረቅ ክርክር ነው።
በአንድ በሆነ ጊዜ መጀመር አለበት ምክንያቱም ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጥራት ላይ እየደረሳ ያለው ጉዳት ሀገሪቱን ከፍተኛ ዋጋ እያስከፈላት ነው። ይሄንን ዝም ብለን ማለፍ አንችልም ብለን እየሄድንበት ነው።
ለተማሪዎችም ፣ ለወላጆችም፣ ለቤተሰብም አንድ (1) ዓመት የመዘጋጃ ጊዜ ሰጥተናል። ለኮሌጆችም ተማሪዎቻቸውን እንዲያዘጋጁበት ጊዜ ሰጥተናል ይሄን ጊዜ በደንብ ተጠቅመው ስራቸውን መስራት አለባቸው።
ይሄ የመውጫ ፈተና የተማሪዎች ፈተና ብቻ አይደለም። ከተማሪዎች በላይ የትምህርት ክፍሎች፣ የኮሌጆች ፣ የዩኒቨርሲቲዎች ፈተና ነው። ምን እያደረጉ ነው ዩኒቨርሲቲዎቹ የሚለውን እንደትምህርት ሚኒስቴር ከዚህ የምናገኘው ፤ እነዚህ ኮሌጆች ፣ ዩኒቨርሲቲዎች በእርግጥም ተማሪዎችን እያበቁ ነው ? ወይስ የዲግሪ ወፍጮ ቤት እንደሚሏቸው ዝም ብሎ ጊዜ እያስቆጠሩ ድግሪ የሚሰጡ ናቸው የሚለውን የምንለይበት ነው።
ስለዚህ የሚቀር አይደለም። ሁሉም እንደማይቀር አውቆ የተሰጠውን የመዘጋጃ ጊዜ በደንብ ተጠቅሞ ትምህርትን በደንብ አስተምሮ በደንብ አስጠንቶ ቢያዘጋጅ ነው የሚሻለው “
ምንጭ፡– ቲክቫህ-ኢትዮጵያ(https://t.me/tikvahethiopia/72499)
ስለዚህም በኢትዮጵያ የሚገኙ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ይህንን የክቡር ሚኒስትር ማሳሰብያና መልዕክት ግምት ውስጥ በማስገባት ከ2015 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ በሚደረገው የከፍተኛ ትምህርት መውጫ ፈተና ዙርያ ለተመራቂ ተማሪዎቻቸው አስፈላጊውን የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችና የፈተና ቅድመ-ዝግጅቶች እንዲከናውኑ ከወዲሁ መልዕከቱን ያሳስባል፡፡